መጽሐፍ ቅዱስ ማታለል በዓይን የሚታይ ቁሳዊ ነገር ብቻ እንዳልሆነ ደጋግሞ ያስጠነቅቃል። ማታለል መንፈሳዊ ነው ፣ ብልህ ነው ፣ እውነትን እንዲመስል ተደርጎ የተቀነባበረ ነው።
📖 "ይህም ድንቅ አይደለም ፤ ሰይጣን ራሱ የብርሃን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣልና።"(2ኛ ቆሮ 11፥14)
ጠላት ሁልጊዜ የሚያስፈራ ሆኖ አይመጣም ፣ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚለው ፣ ማታለል በውበት ፣ በድንቅ ፣ በ"እውቀት" እና በሐሰተኛ ተስፋ ተሸፍኖ ሊመጣ ይችላል።
ውሸት ራሱን በራሱ "እኔ ውሸት ነኝ" ብሎ አያስተዋውቅም።
ሰዎች "በዚህ ሰፊ ዓለም ውስጥ ብቻችንን ነን?" ብለው ከመጠየቃቸው በፊት ፣ መጀመሪያ "እያናገረን ያለው ማን ነው?" ብለው መጠየቅ አለባቸው።
📖 "ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አላቸው፦ ማንም እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ።" (ማቴ 24፥4)
ክርስቶስ በመጀመሪያ ያስጠነቀቀው ስለ ጦርነት አልነበረም ፣ ስለ ተፈጥሮ አደጋም አልነበረም ፣ እርሱ በመጀመሪያ ያስጠነቀቀው ስለ ማታለል ነበር።
ምክንያቱም የሐሰት አባት የሆነው ዲያብሎስ አንድን ትውልድ ለማሳት ጨለማ አያስፈልገውም። እውነትን ሊተካ የሚችል ማራኪ ውሸት ብቻ ነው የሚያስፈልገው።
📖 "እናንተ ከአባታችሁ ከዲያብሎስ ናችሁ... እርሱ ሐሰተኛ የሐሰትም አባት ነውና።"(ዮሐ 8፥44)
በጣም አደገኛው አስመሳይ (counterfeit) በቀላሉ የሚታወቀው ሳይሆን ፣ ለእውነተኛው በጣም የቀረበው ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ምልክቶችና ድንቆች የማታለያ መሣሪያዎች ሊሆኑ እንደሚችሉ ያስጠነቅቃል።
📖 "ሐሰተኞች ክርስቶሶችና ሐሰተኞች ነቢያት ይነሣሉና፥ ቢቻላቸውስ የተመረጡትን እንኳ እስኪያስቱ ድረስ ታላላቅ ምልክትና ድንቅ ያሳያሉ።"(ማቴ 24፥24)
እያንዳንዱ ከተፈጥሮ በላይ የሆነ ክስተት ከእግዚአብሔር ዘንድ የመጣ አይደለም። እያንዳንዱ ምልክት ከሰማይ የመጣ አይደለም። እያንዳንዱ መገለጥ ከእውነት ጋር የተያያዘ አይደለም።
ቅዱስ መጽሐፍ አማኞች በጭፍን ልምምዶችን እንዲያሳድዱ አይነግረንም። ይልቁንም መናፍስትን እንድንመረምር ያዝዘናል።
📖 "ወዳጆች ሆይ ፥ መናፍስትን ሁሉ አትመኑ ፤ ነገር ግን መናፍስት ከእግዚአብሔር እንደ ሆኑ መርምሩ።"(1ኛ ዮሐ 4፥1)
ምክንያቱም ማታለል ሁልጊዜ ክፉ መስሎ አይመጣም።
አንዳንዴ "የበራለት" መስሎ ይመጣል ፣ አንዳንዴ የረቀቀ (advanced) መስሎ ይመጣል።
▫️ አንዳንዴ ውብ ሆኖ ይመጣል።
▫️ አንዳንዴ ደግሞ እንደ ብርሃን ሆኖ ይታያል።
📖 "በዚህም ምክንያት ፥ ሐሰትን ያምኑ ዘንድ እግዚአብሔር የሥሕተትን አሠራር ይልክባቸዋል።"
(2ኛ ተሰ 2፥11)
እውነተኛው ጥያቄ "የባዕድ ፍጥረታት አሉ ወይ?" የሚለው አልነበረም። እውነተኛው ጥያቄ ማታለል አዲስ መልክ ለብሶ ሲመጣ ፣ የሰው ልጅ እውነትን ለይቶ ማወቅ ይችላል ወይ? የሚለው ነው።
0 Comments